News today, Politics

ሩሲያ የከባድ መሳሪያ ተተኳሾችን ከሰሜን ኮሪያ እየገዛች ነው ተባለ

ሩሲያ በበኩሏ ኢኮኖሚዋ በመሻሻል ላይ መሆኑን አስታውቃለች

ሩሲያ የከባድ መሳሪያ ተተኳሾችን ከሰሜን ኮሪያ እየገዛች ነው ተባለ፡፡

ኒዮርክ ታይምስ የአሜሪካ የስለላ ተቋም መረጃን ዋቢ አድርጎ እንደዘገበው ከሆነ ሩሲያ ከዩክሬን ጋር እያደረገች ባለው ጦርነት ምክንያት የጦር መሳሪያ እጥረት አጋጥሟታል፡፡

ሩሲያ የየከባድ ጦር መሳሪያ ተተኳሽ እጥረት ያጋጠማት በአሜሪካ እና አውሮፓ ህብረት በተጣለባት ማዕቀብ እንደሆነ የጠቀሰው ዘገባው እጥረቱን ለማስታገስ ስትልም ከሰሜን ኮሪያ በመግዛት ላይ መሆኗንም ጠቅሷል፡፡

አሁን ላይ ሩሲያ ሮኬቶች እና ሌሎች የረጅም ርቀት የጦር መሳሪያዎችን ለመግዛት ተገዳለች ያለው ዘገባው ጦርነቱ በቀጠለ ቁጥር የጦር መሳሪያውም የበለጠ እያጠራት እንደሚሄድ አመላክቷል፡፡

ባሳለፍነው ሳምንት ሩሲያ ኢራን ሰራሽ ድሮኖችን ከቴህራን መግዛቷን የገለጸው ዘገባው ሩሲያ በአሜሪካ ማዕቀብ ከተጣለባቸው ሀገራት ጋር ግንኙነቷን እያጠበቀች መጥታለችም ብሏል፡፡

የሰሜን ኮሪያ ፕሬዝዳንት ኪም ጆንግ ኡን በሩሲያ ዩክሬን ጦርነት መጀመር ዋነኛዋ ተጠያቂ አሜሪካ እንደሆነች ከዚህ በፊት ተናግረው ነበር፡፡

ፕሬዝዳንቱ ከዩክሬን ወደ ሩሲያ ለተጠቃለሉ ዶምባስ እና ሉሃንስክ ግዛቶች ሉዓላዊነት ቀድመው እውቅና ከሰጡ ሀገራት መካከል ሰሜን ኮሪያ አንዷ ስትሆን ሶሪያ ደግሞ ሁለተኛዋ ሀገር ናት፡፡

ሩሲያ በበኩሏ በአሜሪካ እና አውሮፓ ህብረት ከስድስት ሺህ በላይ ማዕቀቦች ቢጣሉብኝም ማዕቀቦቹ በሩሲያ ኢኮኖሚ ላይ ያደረሱት ተጽዕኖ ሁለት በመቶ ብቻ መሆኑን አስታውቃለች፡፡

የሞስኮ መገበያያ የሆነው ሩብል ከአሜሪካው ዶላር ጋር ሲነጻጸር ከዚህ በፊት ከነበረው ልዩነት መቀነሱን እና የሩሲያ የወጪ ንግድም ጉድለት አለማሳየቱ ተገልጿል፡፡

የፊንላንዱ የምሁራን ስብስብ ተቋም ባወጣው ጥናት ምዕራባዊያን በሩሲያ ላይ የጣሉት ማዕቀብ ጥቂት ጉዳት ብቻ ማድረሱን ጠቅሶ ሩሲያ በስድስት ወራት ውስጥ ብቻ 136 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷን አስታውቋል፡፡

News today, Politics

ፑቲን የቻይና ጦር የተሳተፈበትን “ቮስቶክ 2022” የጦር ልምምድ ላይ መገኘታቸው ተገለጸ

በቮስቶክ 2022 የጦር ልምምድ ከ14 ሀገራት የተውጣጡ 50 ሺህ ወታደሮች ተሳታፊ ሆነዋል

ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ ቻይናን ጨምሮ በርካታ ሀገራት በሚሳተፉበት በግዙፉ የ“ቮስቶክ 2022” የጦር ልምምድ በሚካሄድበት ካቦራቭስክ ወታደራዊ ስፍራ መገኘተቻው የክሬምሊን ቃል አቀባይ ደሚትሪ ፔስኮቭ ገለጹ፡፡

ፕሬዝዳንት ፑቲን በልምምድ ስፍራው የተገኙት ከመከላከያ ሚኒስትሩ ሰርጌይ ሾይጉ እና ከወታደራዊው አዛዥ ቫለሪ ገራሲሞቭ ጋር መሆኑን ቃል አቀባዩ፤ አስታውቀዋል።

ፕሬዝዳንቱ ለሳምንት የዘለቀውን ልምምድ የመጨረሻ ምዕራፍ እንደሚከታተሉ መገለጻቸውም ዘ-ጋርዲያን ዘግቧል፡፡

በሩሲያ አስተናጋጅነት ሲካሄድ የቆየው ግዙፉ ቮስቶክ 2022 የጦር ልምምድ ባሳለፍነው ሳምንት ሀሙስ እንደተጀመረ ሚታወስ ነው፡፡

ቮስቶክ 2022 የሚል መጠሪያ የተሰጠውና በሩቅ ምስራቅ ሩሲያ እና በጃፓን ባህር ላይ ሲካሄድ የቆው ወታደራዊ ልምምድ በነገው እለት እንደሚጠናቀቅም ነው የተገለጸው፡፡

በወታደራዊ ልምምዱ አዘጋጇ ሩሲያን ጨምሮ ቻይና፣ ቤላሩስ፣ ታጃኪስታን፣ ህንድ እና ሞንጎሊያን ጨምሮ በድምሩ 14 ሀገራት ተሳትፈዋል።

በልምምዱ ከሀገራቱ የተውጣጡ 50 ሺህ ወታደሮች የተሳተፉ ሲሆን፤ የረጅም ርቀት ቦምብ ጣይ ጄቶ እንዲሁም የጦር ካርጎ አውሮፕላኖኖች የተካተቱባቸው ከ5 ሺህ በላይ የተለያዩ አይነት የጦር መሳሪያዎች ጥቅም ላይ ውለዋል፡፡

ከጦር መሳሪያዎቹ መካከልም 140 የጦር አውሮፕላኖች እና 60 የጦር መርከቦች እንደሚገኙበትም ነው የሩሲያ መከላከያ ሚኒስቴር መረጃ የሚያመለክተው፡፡

በዚህ የጦር ልምምድ ከሚሳተፉ ሀገራት መካከል አንዷ የሆነችው ቻይና ፤ የጦር ልምምዱ ከወቅቱ የሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት ጋር እንደማይገናኝ መግለጿ ይታወሳል።

መሰል ወታደራዊ ልምምድ ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን፤ የመጀመሪው የጦር ልምምድ እንደፈረንጆቹ 2018 መካሄዱ አይዘነጋም፡፡