News today, Politics, social life

የፌደራል መንግስት እና የህወሓት የድርድር ሂደት ይሳካ ይሆን…?


ምሁራኑ “ህወሓት አሁን ላይ ድርድሩን የጠየቀበት ምክንያት ተገዶ ይሆናል፤ ምክንያት ፈልጎ ሊያቋርጠው እንደሚችል ግምታቸውን አሰቀምጠዋል
በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሽብርተኝነት የተፈረጀው ህወሓት በሀገር መከላከያ ሰራዊት የሰሜን እዝ ማጥቃቱን ተከትሎ ነበር በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት የተጀመረው።


ይህ ጦርነት ላለፉት 23 ወራት የዘለቀ ሲሆን ጦርነቱን ለማስቆም አሊያም ለማሸማገል ራሱ የፌደራል መንግስትን ጨምሮ የአፍሪካ ህብረት የአዉሮፓ ህብረት የተባሩት መንግስታት ድርጅት እና የተለያዩ አካላት ጥረት እያደረጉ ቢሆንም ድርድሩ እስካሁን ሳይሳካ ቀርቷል።


የፌደራል መንግስት እና ህወሓት ድርድር ተስፋ እና ስጋቶች
መንግስት ከህወሃት ጋር ድርድር የሚካሄድበትን ቦታ ለመወሰን ከአፍሪካ ህብረት ጋር እየተነጋገረ መሆኑን አስታወቀ
አሁንም ጦርነት ለማስቆምና እልባት ለመፈለግ እየተደረገ ያለው ጥረት በህወሓት በኩል እንቅፋት እየገጠመው ነዉ ሲል መንግስት በተደጋጋሚ ሲገልጽ ቆይቷል።


መንግስት የሰላም ድርድሩን በአስቸኳይ ለመጀመር የሚያስችል የሰላም ምክረ- ሃሳብን የያዘ ሰነድ ማዘጋጀቱን ይፋ ቢያደርግም፣ ህውሓት በተቃራኒው ከፌደራል መንግስት ጥቃት እንደተከፈተበት በመግለጽ የተኩስ አቁም ስምምነቱ መፍረሱን ገልጾ ነበር።


የፌደራል መንግስትም ህወሓት ከነሀሴ 18 2014 አ.ም ጀምሮ በራያ፣ ወልቃይት ፣ ሰቆጣ እና አፋር ክልል አዋሳኝ ቦታዎች ጥቃት መፈጸሙን አስታውቋል።


ከተጠቀሰው ዕለት ጀምሮም በበትግራይ ክልል እና አማራ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች እንዲሁም በኢትዮ ሱዳን ድንበር አካባቢዎች ላይ ጦርነቱ መቀጠሉ የተገለጸ ሲሆን፤ ህወሓት የዘመን መለወጫ ዕለት ማለትም መስከረም 1 ቀን 2015 ዓ.ም ባወጣዉ መግለጫ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በአፍሪካ ህብረት አደራዳሪነት ለመወያየት እና ግጭቱን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት መዘጋጀቱን አስታውቋል።


ፃድቃን ገብረተንሳይና ጌታቸው ረዳን ያካተተ ከፌደራል መንግስት ጋር ለሚደረገው ድርድር የሚወክሉትን ቡድን ያፈ ያደረገው ህወሓት አለማቀፉ ማኅበረሰብ በታዛቢነትና ድጋፍ በማድረግ እንዲሳተፉ እንደሚፈልግም ገልጿል።


የህወሃትን የእደራደራለሁ መግለጫን ተከትሎ ብዙዎች ተስፋ እና ስጋትን እንደተሰማቸው በተለያዩ መንገዶች ሃሳባቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው።
አል ዐይን አማርኛ የህወሓት ለመደራደር ዝግጁ ነኝ ማለቱን ተከትሎ ስለጉዳዩ ምሁራንን አነጋግሯል።


አቶ አበበ ይርጋ በባህር ዳር ዩንቨርሲቲ ስር ባለው የብሉናይል ውሀ ኢንስቲትዩት የፖለቲካ ሳይንስ እና ዓለም አቀፍ ጥናት መምህር ናቸው፤ የህወሃትን በየትኛውም ቦታ እና ጊዜ በአፍሪካ ህብረት አደራዳሪነት ከፌደራል መንግስት ጋር እደራደራለሁ ማለቱን እንዴት ያዩታል? በሚል ላነሳንላቸው ጥያቄ፤
“ህወሀት ወደ ድርድር እንዲመጣ ለረጅም ጊዜ ሲለመን ነበር፣ ነገር ግን ቅድመ ሁኔታ ሲደርድር እና ሰላም እንዳይፈጠር የቻለውን ሁሉ ሲያደርግ ቆይቷል።

በድንገት ያለ ቅድመ ሁኔታ በየትኛውም ቦታ እደራደራለሁ ማለቱ ከልቡ አይመስለኝም፣ ይሄንን መግለጫም ያወጣው በሎጅስቲክስ እና ፕሮፓጋንዳ ሲያግዙት የቆዩት አካላት አዘውት ነው” ብዬ አስባለሁ ብለዋል።


“በኢትዮጵያ የተለየ ፍላጎት ያላቸው ሀገራት ቁጥራቸው እየጨመረ ነው” የሚሉት መምህር አበበ “ህወሓት እየተሸነፈ ሲመስላቸው እና ተጨማሪ ድጋፍ ለማሰባሰብ እንዲያመቻቸው” ለድርድር ዝግጁ መሆኑን እንዲያሳውቅ ሳያደርገው እንዳልቀረ ግምት እንዳላቸውም ጠቅሰዋል።


“ህወሓት እደራደራለሁ ማለቱ በፌደራል መንግስት ላይ በሚደረግ ጫና ምክንያት መከላከያ ሰራዊት ማጥቃቱን ትቶ አሁን ባለበት ቦታ እንዲቆም ቀስ በቀስም ለአራተኛ ዙር ጦርነት የመዘጋጃ ጊዜ እንደሚያገኝ በማሰቡ ሊሆን ይችላል” ሲሉም ተናግረዋል።


“ድርድሩ የውጭ ጣልቃ ገብነት የተጫነው ይመስላል” የሚሉት መምህር አበበ “ለኢትዮጵያ ዘላቂ መፍትሄ የሚያመጣላት ከድርድሩ ጎን ለጎን በህወሀት ጥቃት እየደረሰበት ያለውን የትግራይ፣ አማራ እና አፋር ክልሎች ህዝብን መታደግ ሲቻል እና መንግስታዊ አገልግሎቶችን መጀመር ብቻ” እንደሆነ ጠቁመዋል።


ሌላኛው በድርድሩ ዙሪያ አል ዐይን አማርኛ ያናገራቸው በጅግጅጋ ዩንቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ እና ዓለም አቀፍ ህግ መምህሩ ሰለሞን ጓዴ ናቸው።


እሳቸው እንዳሉት “በእኔ አመለካከት “ህወሓት አሁን ላይ ድርድሩን የጠየቀበት ምክንያት ተገዶ ይሆናል የሚል እሳቤ አለኝ ምክንያቱም ይፈልጉት የነበረዉ ስትራቴጂካዊ ቦታ ተይዞባቸዋል በዚህም ጫናዉ ሲበዛባቸዉና የጦርነት የበላይነትን ሲያጡ መጀመሪያ አጎንብሶ ከዛም አፈር ልሶ ለመነሳት የሚደረግ ሙከራ ነዉ ብዬ ነዉ የማምነዉ በአንድ ሳምንት ዉስጥ ሽንፈት ካልሆነ በስተቀር ሊፈጠር የሚችል አሳማኝ ምክንያት የለም” ሲሉ ገልጸዋል፡፡


“ህወሓት እንዳለው ወደ ድርድር ከመጣ የታጣቂዎቹ ትጥቅ መፍታት ጉዳይ የድርድሩ ዋነኛ ጉዳይ ይሆናል” የሚሉት መምህር ሰለሞን “ሰላም እንዲመጣ ከተፈለገ መተማመንን የሚያጎለብት ስራ መሰራት አለበት” ብለዋል፡፡


ድርድሩ ፍሬያማ እንዲሆን ከተፈለገ መጀመሪያ ሰላማዊ የሆነ አየር ያስፈልጋል፤ ሉዓላዊነት መከበር አለበት፣ ይህ የሚሆነው ደግሞ የህወሓት ታጣቂዎች ትጥቅ ሲፈቱ እና የሀገር መከላከያ ሰራዊት የሀገሪቱን ዳር ድንበር መቆጣጠር በሚያስችለው መንገድ ሲሰማራ ብቻ እንደሆነም መምህር ሰለሞን አክለዋል።


መምህር ሰለሞን አክለውም የህወሓት የእስካሁኑ የፖለቲካ ባህል ምን ጊዜም እራሱን ብቻ የሚያስቀድም በመሆኑ እደራደራለሁ ማለቱ ከልቡ ሊሆን እንደማይችል ተናግረዋል።


በመንግስትና ህወሓት መካከል የሚደረገው ድርድር ሁሉንም ያሳተፈ ኢንዲሆን የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ም/ቤት ጠየቀ
“ህወሓት እኔ ያልመራሁት ነገር አይደረግም የሚል ድርቅ ያለ መንገድን የሚከተል ድርጅት ነው” የሚሉት መምህር ሰለሞን ድርድር በባህሪው ሰጥቶ መቀበልን እና ሰላማዊ ሁኔታዎችን የሚፈልግ በመሆኑ ድርድሩ የመሳካት እድሉ ጠባብ መሆኑን ጠቁመዋል።


ህወሓት ድርድሩን ቢጀምረው እንኳን ምክንያት ፈልጎ ሊያቋርጠው እንደሚችል ግምታቸውን ያስቀመጡት መምህር ሰለሞን የፌደራል መንግስት በህወሀት ወጥመድ ሊገባ እንደማይገባም አሳስበዋል።


የፌደራል መንግስት ከዚህ በፊት ባወጣው መግለጫ በአፍሪካ ህብረት አደራዳሪነት ከህወሃት ጋር በየትኛውም ቦታ እና ጊዜ እንደሚደራደር ማሳወቁ ይታወሳል።


ለዚህ ድርድርም በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የሚመራ አብይ ኮሚቴ መቋቋሙን እና ሌሎች ንዑስ ኮሚቴዎችም ተቋቁመው ስራ መጀመራቸው መገለጹ አይዘነጋም።

News today, Politics

አፍሪካ ህብረት፣ ተመድ ፣አውሮፓ፣አሜሪካ እና ኢጋድ ህወሓት ባወጣው መግለጫ ዙሪያ ምን አሉ?

አፍሪካ ህብረት “ተፋላሚ ወገኖች በአስቸኳይ ተኩስ ለማቆም እንዲሰሩና የፊት ለፊት ንግግር እንዲያካሄዱ” ጥሪ አቅርቧል

የኢትዮጵያ መንግስት ጦርነቱ በድጋሚ ከመቀስቀሱ በፊት ከህወሓት ጋር ያለቅደመ ሁኔታ በየትኛውም ቦታ እንደሚደራደር መግለጹ ይታወሳል

ህወሓት በአፍሪካ ህብረት ጥላ ስር በሚካሄደው የሰላም ድርድር ሂደት ውስጥ ለመሳተፍ ዝግጁ መሆኑን ትናንት ባውጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

 ህወሓት አቶ ጌታቸው ረዳን እና ጀነራል ጻድቃን ገ/ትንሳኤን ያከተተ ተደራዳሪ ቡድን መሰየሙን ይፋ ማድረጉ ይታወቃል፡፡

    ህወሐት ትናንት ማምሻው በትግራይ የውጭ ግንኙነት ጸ/ቤቱ በኩል ባወጣው መግለጫ ፤ የተሰየመው ተዳራዳሪ ቡድን ወደፊት በሚደረገው ድርድር “የትግራይን መንግስት” የሚወከል ስልጣን ተሰጥቶታለል ብሏል፡፡

    ህወሓት የተሰየመው ተደራዳሪ ቡድን “ሳይዘገይ ወደ ድርድር እንደሚገባ”ም ጠቁሟል፡፡

    የአፍሪካ ህብረት በትግራይ ለተፈጠረው ችግር መፍትሔ “አያመጣም” ሲል የነበረው ህወሓት፤ በትናንትናው መግለጫው ግን በአፍሪካ ህብረት ጥላ ስር በሚደረግ ድርድር ላይ እንደሚሳተፍ ገልጿል፡፡

    ጦርነቱን በድርድር ለመፍታት ሲያደርግ የነበረው የአፍሪካ ህብረት የህወሓት መግለጫ በአወንታ እንደሚመለከው አስታውቋል፡፡

    የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሙሳ ፋኪ፤የትግራይ ክልል መንግስት ግጭቱን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታትና በአፍሪካ ህብረት በሚመራ የሰላም ሂደት ለመሳተፍ ፍቃደኝነት ማሳየቱን በበጎ እንደሚቀበሉት አስታውቀዋል፡፡

    እርመጃው በኢትዮጵያ ሰላም ለማስፈን ጥሩ እድል የሚፈጥር ነው ያሉት ሙሳ ፋኪ፤ “ተፋላሚ ወገኖች በአስቸኳይ ተኩስ ለማቆም እንዲሰሩና በአፍሪካ ህብረት መሪነት የፊት ለፊት ንግግር እንዲያካሄዱ” ጥሪ አቅርበዋል።

    ፊት ለፊት የሚደረገው ድርድር በሁለቱም ወገኖች ተቀባይነት ያላቸው “ዓለም አቀፍ አጋሮችን ያካተተ” እንደሚሆንም ፍንጭ ሰጥተዋል የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበሩ ሙሳ ፋኪ፡፡

    የተባበሩት መንግስታት ድርጅትም ህወሓት በአፍሪካ ህብረት ጥላ ስር በሚደረገው የሰላም ሂደት ላይ ለመሳተፍ ባሳየው ፍላጎት ደሰተኛ መሆኑን ገልጿል፡፡

    የተመድ ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ፤ ሁለቱም ወገኖች ይህንን የሰላም እድል በመጠቀም ግጭትን በማቆም ለውይይት እንዲመርጡ ጠይቀዋል።

    ሁለቱም ወገኖች፤ “በቅን ልቦና እና ሳይዘገዩ በአፍሪካ ህብረት የሚመራውን ሂደት በንቃት እንዲሳተፉና ውይይቱ እንዲካሄድ ምቹ ሁኔታዎችን እንዲፈጥሩ እናበረታታለን” ብለዋል ዋና ጸሃፊው፡፡

    ተመድ በአፍሪካ ህብረት የሚመራውን የሰላም ሂደት ለመደገፍ ያለውን ዝግጁነት በድጋሚ አረጋግጠዋል፡፡

    የሰሜን ኢትዮጵያ ግጭትን በተመለከተ ተደጋጋሚ መግለጫዎች ስያወጣ የነበረው አውሮፓ ህብረት በበኩሉ የትግራይ ክልል መንግስት ጦርነቱ ባስቸኳይ እንዲቆምና በአፍሪካ ህብረት በሚመራው የሰላም ሂደት ለመሳተፍ ዝግጁ መሆኑን መግለጹ በበጎ እንደሚመለከተው ገልጿል፡፡

    የአውሮፓ ህብረት ምክትል ፕሬዝዳንት ጆሴፕ ቦሬል በትዊተር ገጻቸው ባጋሩት ጽሁፍ “እድሉ ሁሉም ሊጠቀሙበት ይገባል” ብለዋል፡፡

    ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ባወጣው መግለጫ ውጊያ ለማቆምና ያልተፈቱ ጉዳዮችን በውይይት ለመፍታት ዝግጁ መሆኑን ማስታወቁን “እናበረታታለን” ያሉት ደግሞ የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አንቶኒ ብሊንከን ናቸው፡፡

     “ኤርትራና ሌሎችም ግጭቱን ከማቀጣጠል ሊቆጠቡ ይገባል” ሲሉም አክለዋል፡፡

    አሜሪካ የኢትዮጵያን አንድነት፣ ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት ትደግፋለች ያሉት ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ አሜሪካ ከሀገሪቱ ጋር ወደነበራት “ጠንካራ አጋርነት” መመለስ እንደምትሻ ም አስታውቀዋል።

    ሌላው የትግራይ ክልል መንግስት ለውይይት ያወጣው መግለጫ ሚበረታታ መሆኑ የገለጸው ደግሞ፤ የኢትዮጵያ ሁኔታን በቅርበት ሲከታታል እንደነበር የገለጸው የምስራቅ አፍሪካ በይነ መንግስታት /ኢጋድ/ ነው፡፡

    የኢጋድ ዋና ጸሃፊው ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ በግጭት ውስጥ ያሉት ኃይሎች በአፍሪካ ህብረት መሪነት ለሚደረግ የሰላም ንግግር ለመመለስ ባሳዩት ፈቃደኝነት መደሰታቸው ገልጸዋል፡፡

    “ኢጋድ ሁለቱም ወገኖች ለተኩስ ማቆምና ለሽምግልና ያሳዩት ቁርጠኝነት ይቀበላል”ም ነውም ያሉት ዋና ጸሃፊው፡፡

    በፌደራል መንግስቱ እና በህወሓት መካከል የነበረው ጦርነት ለወራት ጋብ ብሎ የነበረ ቢሆንም ጦርነቱ በድጋሚ ሊቀሰቀስ ችሏል፤ ጦርነቱን በመጀመር አንደኛቸው ሌላኛቸውን በመክሰስ ላይ ናቸው፡፡

    የኢትዮጵያ መንግስት በድጋሚ ጦርነት ከመቀስቀሱ በፊት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በየትኛው ቦታ ከህወሓት ጋር እንደሚደራደር መግለጹም ይታወሳል፡፡

    ህወሓትም በተመሳሳይ ለድርድር ዝግጁ መሆኑን ቢገልጽም ህወሓት በአፍሪካ ህብረት ላይ እምነት እንደሌላው ሲገልጽ ቆይቶ ነበር፡፡