News today, Politics

የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፤ ቤጂንግ ለናንሲ ፔሎሲ ጉብኝት በዚህ ደረጃ ምላሽ የመትሰጥበት “ምንም ምክንያት የለም” አሉ

ብሊንከን፤ ቻይና ታይዋንን በመክበብ የምታካሂደው ወታደራዊ ልምምድ “ውጥረትን የሚያባብስ” ነው ሲሉ ኮንነዋል

2022/8/5 16:12 GMT

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን

በፔሎሲ ጉብኝት የተበሳጨችው ቻይና “ከአሜሪካ ጋር ስታደረግ የነበረው ወታደራዊ ማቋረጧን” ይፋ እስከማድረግ ደርሳለች

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ቻይና ታይዋንን በመክበብ የምታካሂደው ወታደራዊ ልምምድ ‘ያለው ውጥረት የሚያባብስ’ ነው ሲሉ ኮነኑ።

ብሊንከን የአሜሪካ ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ናንሲ ፔሎሲ ወደ ታይዋን ላደረጉት ጉብኝት ምላሽ ለመስጠት በሚል ቤጂንግ ለጀመረችው ወታደራዊ ልምምድ የምታቀርበው “ምንም ምክንያት የለም” ማለታቸውም ኤፒ ዘግቧል።

ቻይና ባሊስቲክ ሚሳኤሎችን በመተኮስ ተዋጊ ጄቶች እና የጦር መርከቦች በታይዋን ዙሪያ ማሰማራቷን ተከትሎ በዓለም ላይ እጅጉን የመርከብ መስመሮች የሚበዙበት ቀጠና አደጋ እንዳንዣበበበት እየተገለፀ ነው።

ከደቡብ ምስራቅ እስያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር ለመወያየት በበካምቦድያ መዲና ፕኖም ፔን የሚገኙት ብሊንከን ጉዳዩን በማስመልከት በሰጡት መግለጫ “የቻይና ድርጊቶች ያለውን ውጥረት ትርጉም ባለው ደረጃ የሚያባብሱ ናቸው” ሲሉ ተደምጠዋል።

በቅርቡ በኢንዶኔዥያ በተካሄደው ስብሰባ ላይ ዋንግ ዪን፤ በ25 ዓመታት ውስጥ ታይዋንን የጎበኙ ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት ፒሎሲ ወደ ደሴቲቱ ሊጓዙ እንደሚችሉ ነገሬው ነበር ያሉት ብሊንከን፤ የቻይና ድርጊት ከጠበቅነው ውጭ ባይሆንም የተጋነነ ነው ሲሉም ተናግረዋል፡፡

“እውነታው ግን የአፈ ጉባኤዋ ጉብኝት ሰላማዊ ነበር፤ እንደዚህ አይነት የተጋነነ እና ተመጣጣኝ ያልሆነ ወታደራዊ ምላሽ የሚያሰጥበት ምንም ምክንያት የለም” ሲሉም አክለዋል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ብሊንከን ይህን ይበሉ እንጂ፤ ናን ፔሎሲ ቻይና እንደ አንድ ግዛቷ አድርጋ በምትቆጥራት ታይዋን ላይ ያደረጉት ጉብኝት የቤጂንግ ሰዎች ኩፉኛ ማስቆጣቱ እየተገለጸ ነው።

በአሜሪካ ድርጊት እጅጉን የተበሳጨችው ቻይና ከአሜሪካ ጋር ወታደራዊ ትብብሯን ማቋረጧን ከሰዓታት በፊት አስታውቃለች።

ቻይና በውጭ ጉዳይ ሚንስትሯ በኩል በሰጠቸው መግለጫ፤ ቤጂንግ እስካሁን ከከፍተኛ ወታደራዊ ትብብሮች ባለፈ በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ ከዚህ በፊት የነበራትን የከፍተኛ መሪዎች የጋራ ውይይት መድረኮችን ከአሜሪካ ጋር በትብብር ላለመስራት ወስናለች።

እንዲሁም ቻይና ከአሜሪካ ጋር የነበራትን የድንበር አልባ ወንጀል መከላከል፣ ስደተኞችን ማጓጓዝ፣ አደገኛ እጽ ዝውውር መከላከል እና ሌሎች ስምንት የትብብር መስኮችን አቋርጣለች።

ቻይና ሰሞኑን ታይዋንን በጎበኙት የአሜሪካ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ናንሲ ፔሎሲ ላይ ማዕቀብ መጣሏ ይታወሳል።